
ፊሺንግ ዊዝ ኢትዮጲክ በሚል ስም በኢትዮጲክ የተዘጋጀውና በዲሲና አካባቢው ላሉ አንባቢዎችና ቤተሰቦች የተዘጋጀው ወርሀዊ የአሳ ማጥመድ ፕሮግራም ቅዳሜ ሜይ 3 በሰላማዊው የሄይነስ ፖይንት ፓርክ ተከናውኗል።
በፕሮግራሙ ላይም ከ20 በላይ የሚሆኑ ተሳታፊዎች የነበሩ ሲሆን እነዚህ ተሳታፊዎችም በርካታ አሳዎችን አጥምደዋል። ተሳታፊዎች እንደ አምባዛ (ካት ፊሽ)፤ ዋይት ፐርች፤ ሰንፊሽ የመሳሰሉ አሳዎች የተያዙ ሲሆነ በተጨማሪም ግልገል የውኃ ኤሊ (ተርትል) ይዘዋል።

በፕሮግራሙ የተሳተፉ ህጻናትና ታዳጊዎች በልጅ አዕምሯቸው በሚጠይቋቸው በርካታ ጥያቄዎች አማካኝነት በርካታ ትምህርቶችን ስለ አሳ ማጥመድ፤ ስለተፈጥሮ፤ ስለምግብ፤ ስለ መታገስና የመሳሰሉትን ተምረዋል።
የአሳ ማጥመድ ሙያ እንደ ሆቢ አዝናኝና መሳጭ ሲሆን እንደ መሰረታዊ ዕውቀት ደሞ አንድ ሰው ራሱን በችግር ውስጥ ቢያገኘው ራሱን መመገብ የሚያችለው መሰረታዊ ዕውቀት ነው።የዚህ ፕሮግራም ተሳታፊዎችም ይህን መሰረታዊ ዕውቀት ጨብጠው ሄደዋል።
ፊሺንግ ዊዝ ኢትዮጲክ ዋነኛው አላማው በአካባቢያችን ያሉ ቤተሰቦች ያለ ምንም ተጨማሪ አጀንዳ ለመዝናናትና ለመተዋወቅ እንዲሁም ለልጆቻቸው እውቀት እንዲያገኙ በማሰብ የሚተገበር ፕሮግራም ነው። ፕሮግራሙ ነጻና ማንኛውም ሰው ሊሳተፍበት የሚችል ሲሆን በፕሮግራሙ ላይ ከጥሩ ጊዜ ውጪ የሚሸጥም ሆነ የሚለወጥ ነገር የለበትም።
የፕሮግራሙ አዘጋጆችም በሂደት የዚህ ፕሮግራም ተሳታፊዎች በቁጥር የሚበረክቱበትና ከመዝናናት ባለፈ እርስ በእርስ የሚደጋገፉበትና መጠጊያዬ የሚሉትን ማህበረሰብን የሚመሰርቱበት እንደሚሆን አልመው ጀምረውታል።
ማንኛውም ሰው በዚህ ፕሮግራም መሳተፍ የሚፈልግ ይህን ሊንክ በመጫን የቴሌግራም ማህበሩን መቀላቀልና ተጨማሪ መረጃዎችን እንደወጡ ማግኘት ይችላል።